የማለዳ ወግ … እየሳቁ ማልቀስ !

 

Nebiyu Sirakበለጋ እድሜዋ ትዳር መስርታ ሁለት ትጉህ መንታ ልጆች የታደለች እህት ከትዳር ጓደኛዋ ችግር ገጠማት። የ “ተበዳይ ነኝ !” ባይ ወዳጀን ምሬት ደጋግሜ ብሰማም ከቀናት በፊት “በደለኝ! ” ያለችው የትዳር አጋሯ በኮሚኒቲው ሽምግልና ኮሚቴ በኩል ክስ መስራቱን እና የክስ ጥሪ እንደደረሳት ሰማሁ።  ከአሰር አመት በፊት እድሜዋ ገና የ17 አመት እያለ የዛሬ የ12 አመት እድሜ የሆነውን ትልቁን ልጀን ያሳደገችውን እህት የቆየ አብሮነት ትውስታ እያሰብኩ የአለመግባባቱን  ሽምግልና ወደሚከወንበት የጅዳ ኮሚኒቲ ሽምግልናውን ለመታዘብ መጓዝ ጀመርኩ። የያኔዋ ጉብል በኮንትራት ስራ መጥታ ከአሰሪወችዋ ልታመልጥ ከሶስተኛ ፎቅ የወደቀችበትን አሳዝኝ ታሪክ ጀምሮ ከብላቴና  ልጀ ጋር ውለው ሲያድሩ የነበረውን ሁሉ ስደት እና ድህነት በልጅነት እድሜዋ ላይ የጣለውን ህመም አስታወስኩ። እግረ መንገዴን ይህን ሁሉ አውጥቸ አውርጀ ያ ሁሉ አልፎ ለዛሬ ወግ ማዕረግና ለመንታ ልጆች በረከት ያደላትን ፈጣሪ ስራ አስታውሸ ” ለፈጣሪ ምን ይሳነዋል!” ስል አምላኬን አመሰገንኩት!

ወደ ኮሚኒቲው ጽ/ቤት ብዙም ሳልቆይ ደረስኩ። “በደል ደረሰብኝ!” ባይ ቀድማ በቀጠሮዋ ተገኝታለች ። “ልጆቸን ጥላ ሔደች ” ባይ ከሳሽ ባል ዘግይቶ መጣ። ጉዳዩን ለመታዘብ ከባልም ለሚስትም ወገን የመጣን ታዛቢ ሽማግሌወች ሁለት ሶስት ስንሆን ሁላችንም በባልና ሚስት መካከል ሰላም እንዲወርድ ተመኘን። በበዳይ በተበዳይየደረሰወን ሁሉ የሚሰሙት ሽማግሌዎች መሆኑ በጀ ። እኛ በበዳይ በተበዳይም ላይ ያረፈውን የዱላ አሸራ እያነሳን ብንሸመግል ሽምግልናው ፍርሻ በሆነ ነበር ስል ማሰቤ አልቀረም ። ብቻ ኮሚኒቲው ከተመሰረተ በርካታ ጀምሮ በሽምግልናው ረገድ ተመሳሳይ ፋና ወጊ ማህበራዊ ጉዳዮችን በመስራት ላይ ያለው ኮሚቴ አባላት ትናንትም ዛሬም ቤት እንዳይፈርስ፣ ወገን ከወገኑ ሲጋጭ ገጭቱን በወግ በስርአት በማሸማገል ይሰራሉና ብዙውን አስታውሸ አመሰገንኳቸው። ትልቁን ስራ የሚሰራው የዚህ ኮሚቴ አባላት የዚህችን ብላቴና ትዳር ለልጆች ሲባል መታደጋቸውን ከበር ሆነን ሽምግልናውን ስንከታተል ለነበርነውን መልካም የምስራች አበሰሩን !  ባልና ሚስት ልዩትን አስወግደው ለመኖር ተስማምተው ባንድ መኪና ተያይዘው ሲሔዱ የአብራካቸው ክፋዮችን ደስታ መመልከት በራሱ ልዩ የደስታ ስሜትን ይሰጥ ነበር 🙂

ይህንን ሽምግልና ለመታዘብ በጠራራው ጸሃይ በኮሚኒቲው ግቢ ከአንዳንድ ወንድሞቸ ጋር “እንኳን ከእስር በሰላም ወጣህ!” ከሚለው ሰሞነኛ የደስታ መግለጫ ጀምረን በቅርቡ ደጋግሜ ስለማነሳው በግና ፍየል ጠባቂ የነበረ ወንድም የወህኒ አበሳ መጨዋወት ጀመርን። አንዳንዶች ይህ ወንድም ከጅዳ ቆንስል የቅርብ ርቀት በህክምና ላይ እያለ መረጃ ያቀበሉኝ ነበሩና የሰማሁ ያየሁትን ሳጫውታቸው አስደንጋጩን አበሰሩኝ: ( በገዛ ወገኑ አካሉ የፈረሰው ወንድም ሊሴ ፖሴ ተሰርቶለት ከሳምታት በፊት ወደ ሃገር መግባቱን ነበር ያረዱኝ: ( መረጃው በሽምግልናው የተሰማኝን ደስታየን ነጠቀኝ 😦  በስጨት ብየ ወደ ቤቴ አመራውሁ … ይህንንስ ዝም በሚል ቁሽት ተጀቡኘ  !

ከድብደባው ጀምሮ እስከ ህክምናውና በቅርብ እስከ ነበረው የተቃወሰ የዚህ ግፉ ወንድም የሰበሰብኩትን መረጃዎችን ” ህይዎት በብሪማን ብየ ለሁለት ወራት ያለማቋረጥ በያዝኩት ማስታወሻ ሰፍሯል ። እሱኑ እያገላበጥኩ ባየውም ህመም እንጅ ያገኘሁት ፋይዳ የለም ! ደግሞስ ምን ማድረግ ይቻለኛል ?  ግለሰቦች ምንም ማድረግ ባይቻለን የመንግስት ተወካዮቻችን በዜጎች ላይ እንዲህ ግፍ ሲፈጸም ጉዳዩን ለሚመለከተው አካል ማድረስ አለመቻላቸው ውስጤን ቢያደማው ሙሉ ታሪኩን ቀን ሲወጣ በመረጃ አስደግፊ እስካቀርበው ከደማው ለቤ ይህችን ታክል ማለትን ወደድኩ …

ወዳጆቸ ሆይ !  የዚህ ወንድም ወደ ሃገር ቤት ገባ በሚል የደረሰኘ መረጃው እርግጠኛ መሆኑን ገና አላረጋገጥኩም።  መረጃው አውነት ሆኖ ከምስኪን ወገኖቹ ተቀላቅሎ ከሆነ ግን ይህን ወንድም ከንፈር ከመምጠጥ ባለፈ ልንደግፈው፣ በማቋቋሙና ከጎኑ ልንቆም ግድ ይለናል!  በዚህ ረገድ መረጃውን ከማረጋገጥ ጀምሮ አድራሻውን አፈላልጋለሁ ። እኛ በህግ ፊት ቀርበን መሞገት አይቻለንም ፣ ይህን ማድረግ እየቻሉ ያላደረጉት በጸጸት ይንደዱ ! እኛ ግን ከሁሉም በላይ “ነግ በእኔን ” ትተን ለፈጣሪ ስንል  ሰብአዊነት ተሰምቶን የምንችል ሁላችንም የአርዳታ እጃችን እንድንዘረጋ አደራ እላችኋለሁ  !

( ሁለት አይኑ በድብደባ የጠፋውንና ፊቱ ሙሉ በሙሉ አይሆኑ የሆነው ወንድም ከሰውነት ተራ ያወጣ ጉዳት የሚያሳዩ ፎቶዎች በእጀ ላይ ቢገኙም ሁሉንም ልጥፍና ላሳዝናችሁ ግን አልሻም! )

አንድየ ይታረቀን  ! ቸር ያሰማን  !

Leave a comment