የሰሞኑ የሥልጠና ፓለቲካ

የስምኦን ልጅ በረከት ከመክተብም አልፎ የሃገሪቷን ልሂቃን ኢንዶክትሪኔት እያደረገ ይገኛል። እስከማስታውሰው ድረስ የበረከት የመጨረሻ ህልም በዩንቨርስቲ ተጋባዥ መምህር ሆኖ ሌክቸር መስጠት ነበር። እነሆ!የልብን መሻት በማየት በላቀ ደረጃ የሚሰጠው ” ልማታዊ መንግሥት ” የሌክቸረሮች ሌክቸረር አደረገው። ርግጥ የድርጅቱ ከአጠገቡ አለመኖርም ህልሙን ያለጊዜው እንዲሳካ ሳያግዘው አልቀረም ። እኔ እምለው እሱ ባይኖር ኖሮ ማን ጵፎ ማን ያሰለጥን ነበር? አደራችሁን! ዶክተር ደብረጲዬን ብላችሁ የሀይሌን ልብ እንዳታቆሟት። የሀይሌ ልብ ከቆመ ሀገሪቷ በሁለት አመት ውስጥ ሁለት ጊዜ መስቀለኛ መንገድ ላይ ስለምትቆም ማናችንም አንፈቅድም ። ከሀይሌ ጋር ያላባራ ፀብ የገጠመው በረከትም ቢሆን!
ወደ ቁምነገሩ ልመለስ ።ወዳጄ ሰነዶቹን ሲልክልኝ ከተለመደው ውጭ አዲስ ነገር አይኖረውም በማለት ትኩረት አልሰጠሁትም ነበር። አላነበብኩትም ላለማለት ብቻ ስልኬን ከፈትኩ። ከሰነዶቹ ውስጥ ” የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ትግላችንና ፈተናዎቹ” የሚለው ቀልቤን ሳበው ። አንብቤ ስጨርስ ውስን ነጥቦችን መዝዤ በማውጣት ከትላንትናው አስተሳሰብ ጋር ማገናዘብ ጀመርኩ። እናም ስልኬን አውጥቼ የሚከተሉትን ቁምነገሮች ለመክተብ በቃሁ ፣
1• Paradigm Shift
bereket
ይህ ሰነድ ስርነቀል የአስተሳሰብ ለውጥ ያመጣው በስርአቱ አደጋ ላይ ነው። ድርጅቱ ከመሬት በታች ከመዋሉ በፊት በጳፉቸው ድርሳናትም ሆነ ገድሎች የስርአቱ አደጋ በዋነኛነት የሚመነጨው ከውስጥ ነበር። ቦናፓርቲዝም፣ ጥገኛ ዝቅጠት ፣ የመበስበስ አደጋ፣ እንደ አሣ ከጭንቅላቱ መሽተት ፣ ሙስና፣ ጠባብነት እና ትምክህት፣አድርባይነት… ወዘተ የውስጥ አደጋዎቹ መገለጫዎች ነበሩ።
ዛሬ የስምኦን ልጅ ምስጋና ይግባውና በዚህ ጉዳይ ላይ ስር ነቀል የአስተሳሰብ ለውጥ በማድረግ ( ” የአስተሳሰብ እድገት” አለማለቴን ልብ ይሏል) የስርአቱ አደጋ ከኢህአዴግ ውጭ እንደሚመነጭ ያበስራል። ለዚህ እማኝ እንዲሆን በገፅ 24 ላይ ፣
“… በስልጣን ላይ ሆኖ አገሪቷን የሚያምሰ የትምክህት ሀይል የለም። … በሥልጣን ላይ ሆኖ አገሪቷን የሚያተራምስ የጠባብነት ሐይል የለም።” በማለት ይገልጻል።
ለዚህ አስተሳሰብ ማጠናከሪያ የሚሆነው በዚሁ ገጵ ላይ ፣
“… ይህ መሰረታዊ ጉዳይ እንደተጠበቀ ሆኖ በሥልጣን ላይ ባለው ፓርቲና በመንግሥት መዋቅሮች የትምክህትና የጠባብነት አስተሳሰብን የሚያራምዱ ግለሰቦች አሉ።” በማለት ችግሩን በግለሰብ ደረጃ የሚገለፅ እንደሆነ ያሰምርበታል ።
ታዲያ የስርአቱ አደጋ የትነው ያለው?
2• ማነው ባለሳምንት?

የበረከት ማስታወሻ በኢህአዴግ ውስጥ ሰርጐ ገቦች መኖራቸውን አምኗል ። እነዚህ ሰርጐ ገቦች ከሌሎች ጋር በመቀናጀት ስርአቱ ላይ ፈተና እንደደቀኑበት በሚከተለው መልኩ በገፅ 24 ላይ ጠቅሶታል፣
“… ውጭ ሆነው ስርአቱን ለማፍረስ ከሚንቀሳቀሱ የትምክህትና ጠባብነት ሐይሎች ጋር በመቀናጀት ልዩ ልዪ ፈተናዎችን በመደቀን ላይ ይገኛሉ።”
ይህቺ አንቀጵ በንዴት እንደተጳፈች ታስታውቃለች። የንዴቱ ምንጭ የቅርብ ግዜውን የኦቦ አዲሱን እና የራሱን ቅሌት በማስታወስ የተጳፈች ትመስላለች ።
ኦቦ በንዴት ውስጥ ሆኖ፣
” … ሁለት ሶስተኛው መምህር የእኛ አባል ሆኖ በራሳችን ላይ ይሰለፉል” ነበር ያለው። የስምኦን ልጅ ደግሞ ቁርሴን ስበላ በሚል መንደርደሪያ የቅርብ ጓደኞቹ ሳይቀሩ ” ምርጫ የማይደርስ መስሎሀል?” በማለት እንደዛቱበት ተናግሯል ።
እናም አጨዳው ይቀጥላል ። ከበረከት ሰነድ ለመረዳት እንደሚቻለው ለመጠረግ የተዘጋጁት የአማራና ኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ የኢህአዴግ አባላት ናቸው።
ጠራጊው ማን ይሆን? ጠረጋው እስከየት ድረስ ይዘልቃል?

3• ትምክህት Vs አማራ
የበረከት ሰነድ በሚያስደነግጥ ሁኔታ ትምክህት ለአማራ ብሔረሰብ ተወላጆች ልዩ ስጦታ በማድረግ አቅርቧል። ሌላው ቀርቶ ከአማራ ክልል ውጭ በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ የሚደርሰው ችግር ዋነኛ መንስኤ ” ከትግራይ የፈለቀው ገዥ መደብ እና ባለሟሎቹ” መሆኑን በመካድ በገፅ 29 ላይ፣
“… የዚህ አይነት ችግር ሲፈጠር በተጨባጭ የሚታወቁት መንስኤዎች ሁለት ናቸው ።አንዱ በራሳቸው የአማራ የተወሰኑ ወላጆች ዘንድ የሚታይ ችግር ሲሆን ፣ሌላው በሚኖርበት ህዝብ የተወሰነ ማህበረሰብ ዘንድ የሚታይ ችግር ወይም ድክመቶች ናቸው” በማለት ይገልጻል ።
አቶ በረከት ወክየዋለው የሚለውን የአማራ ብሔረሰብ በሌላ ክልል ሲኖር፣ የሚኖርበትን ብሄር ብሔረሰብ የሚንቅ፣የማያከብር፣ ማንነቱን የማይቀበልና የመጉዳት አዝማሚያ ያለው በማለት ይፈርጀዋል። ( የበረከትን ፅሁፍ ላለመዳችሁ አንባቢያን ” የተወሰኑ” ፣” ጥቂት”፣ ” እዚህ ግባ የማይባሉ”፣” እፉኚት” … ወዘተ የሚሉ የፊት ቅጥሎች (prefix) ካያችሁ እንደ ዳቦ ስም ውሰዷቸው)

4• ” የእኩልነት ጨዋታ ”
የበረከት ማስታወሻ በገፅ 34 ላይ ” የብሔር እኩልነት በተከበረበት የሌለ በማስመሰል።… በፌደራል ደረጃ እኩል የመሳተፍ መብት በተከበረበት በዚሁ አዲሱ ዘመን እነዚህ መብቶች እንደሌሉ ” በማለት የጠባብ ሐይሎች ተገቢ ያልሆነ ወቀሳ እንደሚያቀርቡ ያስገነዝባል። ይህን የአቶ በረከት መከራከሪያ እንደ ቅቡል ወስደን የሚከተለውን ጥያቄ እናንሳለት፣
* በፌደራል ደረጃ አራቱ ታዳጊ ክልሎች ዘወትር የውክልና ጥያቄ እንደሚያቀርቡ የዘወትር ሪፓርትህ ነው። እናም ስንት ሚኒስትር፣ ዴሬክተር፣ ስራ አስፈጳሚ… አለ? ( ከሀያ ሶስት አመት የሥልጣን ዘመን በኋላ የድሮውን መከራከሪያ እንዳታቀርብና እጄን በአፌ ላይ እንዳላገኘው።)
* አቶ በረከት ሠራዊቱን ለማመጣጠን እንደተቻለ በገፅ 31 ላይ አስታውቀሀል። ታዲያ ለምን የሐይማኖት ስብጥርን በአሃዝ አስደግፈህ እንዳቀረብከው የሰራዊቱን የአመራር ደረጃ በዛው መልኩ አቅርበህ አፉችንን አታዘጋንም?

5• አዲሳአባ

አቶ በረከት ያዘጋጀው ሰነድ ከአዲሳአባ ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ የነበረው ችግር ፣የሁከቱ ምክንያት እና መገለጫ የጠባብ ሐይሎች ዘመቻ እንደሆነ በገፅ 33 ላይ ያሳውቃል ። በርግጥ የኦህዴድ አመራር አባላትና የኦሮሚያ ሚዲያ ( ሳታቫኦ) እጃቸው አለበት ብሎናል። ከዚህ በተጨማሪም በዚሁ ገጵ ላይ፣
“… በአዲስ አበባ የፌደራል ዋና ከተማነትና በኦሮሚያ ክልላዊ ጥቅም መካከል ይህ ነው የሚባል ግጭት የለም” ይለናል ።
ጥያቄ አንድ: ማስተር ፕላኑ መጀመሪያ በተባለው መልኩ ሳይሸራረፍ ይፈፀማል ማለት ነው?
ጥያቄ ሁለት: የጥቅም ግጭቱ ከሌለ የኦሮሚያ ልዪ መብት እስከ አሁን ለምን አልተደነገገም?
ጥያቄ ሶስት: ችግር የፈጠሩት የኦህዴድ ባለሥልጣናት እነማን ናቸው? ( በነገራችን ላይ ኦቦ ጁነዲን ሳዶ አትላንታ ለሚገኙ ወዳጆቹ ” ያ! ማኪያቬሊ ሃገሪቷን የማትወጣበት አዘቅት ከቶ ሞተ ” እያለ እንደሚናገር ሰምተሀል መቼስ?)

6• ቤኔሻንጉል vs የደች በሽታ ( Dutch Disease)

አባይን መገደብ የማን አስተሳሰብ ነበር? የሚለው ጥያቄ ለጊዜው ይቆየንና ግድቡ እየተሠራበት ካለው ቦታ አንጳን አንድ ጥያቄ እናንሳ። በሕገመንግሥቱ የመገንጠል ጥያቄ ሊነሳ የሚችለው ከመከፉት( መበደል) ብቻ ሳይሆን ” የአይናችሁ ቀለም አላማረኝም፣ ብቻዬን መኖር ፈለኩ ” ከሚል ጫፍ የረገጠ ፈንጠዝያም ሊነሳ እንደሚችል ባለራእዪ መሪ ደጋግመው ነግረውናል። እናም ቤኔሻንጉሎች ” የመገንጠል ጥያቄ” ቢያነሱ ምላሻችን ምን ይሆናል?
( ምክር ቢጤ:የተሐድሶ ጊዜ ደጋግመን የዘመርናትን ” የደቾች በሽታ” በካሪኩለማችን ቢካተት ።)

7• የተዘነጋ ፍረጃ
ጓድ በረከት ለአማራ ህዝብ ትምክህት ፣ ለኦሮሞ ህዝብ ደግሞ ጠባብነት የሚባሉ ኢህአዴጋዊ ጥብቆ አጠለክ። የትግራይ ህዝብ የትኛውን ይልበስ?

Leave a comment