ግንቦት ሰባትን የምደግፈው ሻዕቢያን ተስፋ ስለማደርግ ኣይደለም ( ሄኖክ የሺጥላ )

የግንቦት ሰባትን ትግል እደግፋለሁ ። ትግሉን የምደግፈው ሻዕቢያን ተስፋ ስለማደርግ ሳይሆን በነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ብልሃት ላይ ተስፋ ስለማደርግ እንጂ !
ግንቦት ሰባትን የምደግፈው የ ሻዕቢያ ቅንነት ልቤን ሰልቦት ሳይሆን የኢትዮጵያ ህዝብ ለለውጥ ያለውን ተነሳሽነት በጥልቀት ስለምረዳ ። እናውራ ከተባለ የዘንድሮ ሻዕቢያ ከድሮ ሻቢያ የሚለየው የዘንድሮው ተስፋ መቁረጡ ብቻ ነው። ተስፋ የቆረጠ ደሞ ብልህ ከሆነ ቀጣዩን የፖለቲካ ኣካሄድ ይረዳል ። ከቻለ ኣቀጭጮ እያባበለ ኣንድ እርምጃ እንዳትራመድ ኣድርጎ ይይዝሃል ( ያየነው ነው ፥ ምናልባት እየሆነም ያለ ይሆናል ) ፥ የማይችል ከሆነ ድጋፉን ይሰጥሃል ። እስከሚገባኝ ግን ሻዕቢያ የመጀመሪያውን ስትራቴጂ ይጠቀምበት የነበረው ዘመኑ ያለቀ ይመስለኛል ። በዚያ ዘመን ኤርትራ የገቡ ተገድለዋል ታስረዋል ( የኔን ወንድም ጨምሮ) ። ዳንኤል ክብረት እንዳለው ያ የጆሮ ዘመን ነበር ። ኣሁን ትግሉ ከጆሮ ዘመን ወደ ቀንድ ዘመን ከፍ ብሏል ፥ ይህንን ደሞ ሻዕቢያ ጠንቅቆ ይረዳል ። ኣይደለም በደባ በሴራ እና በተንኮል በጥንቆላም ሊያቆመን የማይችልብችት ደረጃ ላይ እንደደረስንም ያውቃል ። ስለዚህ በጥንካሬያችን ተረቶ ወይም ተስፋ ቆርጦ ፥ ትግላችንን ባይደግፍ እንኳ እንደማያደናቅፍ መገመት እችላለሁ። ይህ 25 የጭቆና ኣመታት የወለዱት ድል ነው ። የተሸነፍን ቢመስልም እርግጥ በቡዙ ነገር ኣሸንፈናል ። ወደ ውስጥ መመልከት ለቻለ ። ዛሬ በኦሮሚያ ፥ በጎንደር ፥ በጋምቤላ ፥ በኣርባምጭ እና ወዘተ እየተካሄደ ያለው ትግል ተሸንፈንም ቢሆን ማሸነፋችንን ያሳየንበት ነው ። ይህ ሻዕቢያን ይጠፋዋል ማለት ዘበት ነው።

በኔ እይታ ማንም ታጋይ ነኝ ባይ ሻቢያን ኣምኖ ወይም ተስፋ ኣድርጎ ትግል የጀመረ ኣይመስለኝም ። እርግጥ ኣንዳንድ የፖለቲካ ዶቃዎች ምክንያቱን ወደዚያ ጫፍ ሲገፉት ኣያለሁ ። ይህ ስህተት ይመስለኛል። እኔ ስገምት ብርሃኑ ነጋ ኤርትራ የገባው ኣንደኛ “ኤርትራ ለኢትዮጵያ ስለምትቀርብ ፥ በደምም በመልካ ምድራዊ ኣቀማመጥም ( ይህንን ማስረዳት ያስቃል ) ፥ ሁለተኛ እና ዋነኛው ምክንያት ግን ሻቢያ ተቃዋሚዎችን ሰብስቦ ወያኔን ከማስፈራራት ፥ እራሱም ሻቢያ በፖለቲካ ሂደቱ ወደ መፍራት እና በራሱ ፖለቲካ መጃጃት ደረጃ ላይ ስለደረሰ በእርግጥ ጥቅሜን ሊያስጠብቁ ይችላሉ ከሚላቸው ኣካላት ጋ መስራቱ ኣዋጭ ሃሳብ ነው ብሎ ኣስልቶ ሳይሆን ኣይቀርም ባይ ነኝ።

ስለዚህ ስለ ትግሉ ሳስብ ሻዕቢያን ስለ ማመን ወይም ኣለማመን ማሰብ ኣልሻም ። ብናስብ እንኳ መነሻ ነጥቤ የሚሆነው « ኣላምነውም » ብዬ መነሳቱ ነው።
ሻዕቢያን ምን እንደሚመስል የማያውቅ ካለ ልጁን ወያኔን ይይ! ያ ማለት ግን ኣይጠቅምም ማለት ኣይደለም ፥ ያ ማለት የስትራቴጂ ለውጥ ኣይስፈልግም ማለት ኣይደለም ፥ ያ ማለት በነሱ ጭንቅላት ማሰብ ያቅተናል ማለት ኣይደለም ፥ ያ ማለት ሁል ጊዜ እንደበለጡን እና እንዳሸነፉን ይኖራሉ ማለት ኣይደለም ። ማለት ነው ብሎ የሚያስብ ካለ በእርግጥም የኢትዮጵያን ክብር የማያውቅ ነው ፥ ታሪኩን የማይረዳ ነው። ለውጥ መምጣጡ ኣይቀርም ፥ ሻቢያ ደሞ ከግርጌ መውደቅ ኣይፈልግም ። እኛ ደሞ ከጭንቅላቱ ቀና ለማለት እኛነታችንን ኣሳምነን ትግል ማድረግ ግድ ይላል ። ስለዚህ የግንቦት ሰባትንም ትግል እደግፈዋለሁ ። ግን እየደገፍኩት ኣረጃለሁም ማለት ኣይደለም!”

.zehabesha

posted by tigi flate

 

Leave a comment